Psalms 34

የእግዚአብሔር ፍትሕ ውዳሴ

እንደ እብድ ሆኖ አቤሜሌክ ፊት በመቅረቡ ተባርሮ በወጣ ጊዜ የዘመረው፤ የዳዊት መዝሙር።

1 እግዚአብሔርን ሁልጊዜ እባርከዋለሁ፤
ምስጋናውም ዘወትር ከአፌ አይለይም።
2ነፍሴ በእግዚአብሔር ተመካች፤
ትሑታንም ይህን ሰምተው ሐሤት ያደርጋሉ።
3ኑና ከእኔ ጋር እግዚአብሔርን አክብሩት፤
ስሙንም በአንድነት ከፍ ከፍ እናድርግ።

4 እግዚአብሔርን ፈለግሁት፤ እርሱም መለሰልኝ፤
ከፍርሀቴም ሁሉ አዳነኝ።
5ወደ እርሱ የሚመለከቱ ያበራሉ፤
ፊታቸውም ከቶ አያፍርም።
6ይህ ችግረኛ ጮኸ፤ እግዚአብሔርም ሰማው፤
ከመከራውም ሁሉ አዳነው።
7 እግዚአብሔርን በሚፈሩት ዙሪያ የእግዚአብሔር መልአክ ይሰፍራል፤
ያድናቸዋልም።

8 እግዚአብሔር ቸር መሆኑን ቀምሳችሁ እዩ፤
እርሱን መጠጊያ የሚያደርግ ምንኛ ቡሩክ ነው!
9እናንተ ቅዱሳኑ፤ እግዚአብሔርን ፍሩት፤
እርሱን የሚፈሩት አንዳች አያጡምና።
10አንበሶች ሊያጡ፣ ሊራቡም ይችላሉ፤
እግዚአብሔርን የሚሹ ግን መልካም ነገር አይጐድልባቸውም።
11ልጆቼ ሆይ፣ ኑ፤ ስሙኝ፤
እግዚአብሔርን መፍራት አስተምራችኋለሁ።
12ሕይወትን የሚወድድ፣
በጎውንም ያይ ዘንድ ዕድሜን የሚመኝ ማን ነው?
13አንደበትህን ከክፉ ነገር ከልክል፤
ከንፈርህንም ከሽንገላ ጠብቅ።

14ከክፉ ሽሽ፤ መልካሙንም አድርግ፤
ሰላምን ፈልጋት፤ ተከተላትም።
15 የእግዚአብሔር ዐይኖች ወደ ጻድቃን ናቸው፤
ጆሮዎቹም ለጩኸታቸው ክፍት ናቸው።
16መታሰቢያቸውን ከምድር ለማጥፋት፣
የእግዚአብሔር ፊት በክፉ አድራጊዎች ላይ ነው።

17ጻድቃን ሲጮኹ፣ እግዚአብሔር ይሰማቸዋል፤
ከመከራቸውም ሁሉ ያድናቸዋል።
18 እግዚአብሔር ልባቸው ለተሰበረ ቅርብ ነው፤
መንፈሳቸው የተሰበረውንም ያድናቸዋል።

19የጻድቅ መከራው ብዙ ነው፤
እግዚአብሔር ግን ከሁሉም ያድነዋል።
20ዐጥንቶቹን ሁሉ ይጠብቃል፤
ከእነርሱም አንድ አይሰበርም።

21ኀጢአተኞችን ክፋት ይገድላቸዋል፤
ጻድቃንን የሚጠሉ ይፈረድባቸዋል።
22 እግዚአብሔር የባሪያዎቹን ነፍስ ይቤዣል፤
እርሱንም መጠጊያ ያደረገ አይፈረድበትም።
Copyright information for AmhNASV