Proverbs 15

1የለዘበ መልስ ቍጣን ያበርዳል፤
ክፉ ቃል ግን ቍጣን ይጭራል።

2የጠቢብ አንደበት ዕውቀትን ታወድሳለች፤
የተላሎች አንደበት ግን ቂልነትን ያፈልቃል።

3 የእግዚአብሔር ዐይኖች በሁሉም ስፍራ ናቸው፤
ክፉዎችንም ደጎችንም ነቅተው ይመለከታሉ።

4ፈውስ የምታመጣ ምላስ የሕይወት ዛፍ ናት፤
አታላይ ምላስ ግን መንፈስን ትሰብራለች።

5ተላላ የአባቱን ምክር ይንቃል፤
መታረምን የሚቀበል ግን አስተዋይነቱን ያሳያል።

6የጻድቃን ቤት በብዙ ሀብት የተሞላ ነው፤
የክፉዎች ገቢ ግን መከራን ታመጣባቸዋለች።

7የጠቢባን ከንፈር ዕውቀትን ታስፋፋለች፤
የተላሎች ልብ ግን እንዲህ አይደለም።

8 እግዚአብሔር የክፉዎችን መሥዋዕት ይጸየፋል፤
የቅኖች ጸሎት ግን ደስ ያሰኘዋል።

9 እግዚአብሔር የክፉዎችን መንገድ ይጸየፋል፤
ጽድቅን የሚከታተሉትን ግን ይወድዳቸዋል።

10ከመንገድ የሚወጣ ሰው ጥብቅ ቅጣት ይጠብቀዋል፤
ዕርምትን የሚጠላ ይሞታል።

11ሲኦልና የሙታን ዓለም
በዕብራይስጡ ሲኦልና አባዶን ይላል።
በእግዚአብሔር ፊት የተገለጡ ናቸው፤
የሰዎች ልብማ የቱን ያህል የታወቀ ነው!

12ፌዘኛ መታረምን ይጠላል፤
ጠቢባንንም አያማክርም።

13ደስተኛ ልብ ፊትን ያፈካል፤
የልብ ሐዘን ግን መንፈስን ይሰብራል።

14አስተዋይ ልብ ዕውቀትን ይሻል፤
የተላላ አፍ ግን ቂልነትን ያመነዥካል።

15የተጨቈኑ ሰዎች ዘመናቸው ሁሉ የከፋ ነው፤
በደስታ የተሞላ ልብ ግን የማይቋረጥ ፈንጠዝያ አለው።

16 እግዚአብሔርን ከመፍራት ጋር ያለ ጥቂት ነገር፣
ሁከት ካለበት ትልቅ ሀብት ይበልጣል።

17ፍቅር ባለበት ጐመን መብላት፣
ጥላቻ ባለበት የሰባ ፍሪዳ ከመብላት ይሻላል።

18ግልፍተኛ ሰው ጠብ ያነሣሣል፤
ታጋሽ ሰው ግን ጠብን ያበርዳል።

19የሀኬተኛ መንገድ በእሾኽ የታጠረች ናት፤
የቅኖች መንገድ ግን የተጠረገ አውራ ጐዳና ነው።

20ጠቢብ ልጅ አባቱን ደስ ያሰኛል፤
ተላላ ሰው ግን እናቱን ይንቃል።

21ማመዛዘን የጐደለው ሰው ቂልነት ያስደስተዋል፤
አስተዋይ ሰው ግን ቀጥተኛውን መንገድ ይከተላል።

22ምክር ሲጓደል ዕቅድ ይፋለሳል፤
በብዙ አማካሪዎች ግን ይሳካል።

23ሰው ተገቢ መልስ በመስጠት ደስታን ያገኛል፤
በወቅቱም የተሰጠ ቃል ምንኛ መልካም ነው!

24ወደ ሲኦል
ወይም መቃብር
ከመውረድ እንዲድን፣
የሕይወት መንገድ ጠቢቡን ሰው ወደ ላይ ትመራዋለች።

25 እግዚአብሔር የትዕቢተኛውን ቤት ያፈርሰዋል፤
የመበለቲቱን ዳር ድንበር ግን እንዳይደፈር ይጠብቃል።

26 እግዚአብሔር የክፉውን ሰው ሐሳብ ይጸየፋል፤
የንጹሓን ሐሳብ ግን ደስ ያሰኘዋል።

27ስስታም ሰው በቤተ ሰቡ ላይ ችግር ያመጣል፤
ጕቦን የሚጠላ ግን በሕይወት ይኖራል።

28የጻድቅ ሰው ልብ የሚሰጠውን መልስ ያመዛዝናል፤
የክፉ ሰው አፍ ግን ክፋትን ያጐርፋል።

29 እግዚአብሔር ከክፉዎች ሩቅ ነው፤
የጻድቃንን ጸሎት ግን ይሰማል።

30ብሩህ ገጽታ ልብን ደስ ያሰኛል፤
መልካም ዜናም ዐጥንትን ያለመልማል።

31ሕይወት ሰጭ የሆነውን ተግሣጽ የሚሰማ፣
በጠቢባን መካከል ይኖራል።

32ተግሣጽን የሚንቅ ራሱን ይንቃል፤
ዕርምትን የሚቀበል ግን ማስተዋልን ያገኛል።

33 እግዚአብሔርን መፍራት ጥበብን መማር ነው፤
ወይም ጥበብ እግዚአብሔርን መፍራት ታስተምራለች።

ትሕትናም ክብርን ትቀድማለች።
Copyright information for AmhNASV