Psalms 48

የእግዚአብሔር ተራራ ጽዮን

ዝማሬ፤ የቆሬ ልጆች መዝሙር።

1 እግዚአብሔር ታላቅ ነው፤
በአምላካችን ከተማ በተቀደሰው ተራራ ከፍ ያለ ምስጋና ይገባዋል።

2የምድር ሁሉ ደስታ የሆነው፣
በሰሜን በኩል
ጻፎን የሚለው የዕብራይስጡ ቃል የተቀደሰ ተራራን ወይም የሰሜንን አቅጣጫ ሊያመለክት ይችላል።
በርቀት የሚታየው፣
በከፍታ ላይ አምሮ የደመቀው የጽዮን ተራራ፣
የታላቁ ንጉሥ ከተማ ነው።
3እግዚአብሔር በአዳራሾቿ ውስጥ ሆኖ፤
ብርቱ ምሽግ እንደ ሆናት አስመስክሯል።

4እነሆ፤ ነገሥታት ተባብረው መጡ፤
አንድ ላይ ሆነውም ገሠገሡ።
5አይተውም ተደነቁ፤
ደንግጠውም ፈረጠጡ።
6ምጥ እንደ ያዛት ሴት፣
በዚያ ብርክ ያዛቸው።
7የምሥራቅ ነፋስ የተርሴስን መርከብ እንደሚሰባብር፣
አንተ አብረከረክሃቸው።

8እንደ ሰማን፣
በሰራዊት አምላክ ከተማ፣
በአምላካችን ከተማ፣
እንዲሁ አየን፤
እግዚአብሔር ለዘላለም ያጸናታል። ሴላ

9አምላክ ሆይ፤ በቤተ መቅደስህ ውስጥ ሆነን፣
ምሕረትህን እናስባለን።
10አምላክ ሆይ፤ ምስጋናህ እንደ ስምህ፣
እስከ ምድር ዳርቻ ይዘልቃል፤
ቀኝ እጅህም ጽድቅን የተሞላች ናት።
11ስለ ፍርድህ፣
የጽዮን ተራራ ሐሤት ታድርግ፤
የይሁዳ መንደሮችም ደስ ይበላቸው።

12በጽዮን አካባቢ ተመላለሱ፤ ዙሪያዋንም ሂዱ፤
የጥበቃ ግንቦቿንም ቍጠሩ፤
13ለሚቀጥለው ትውልድ ትናገሩ ዘንድ፣
መከላከያ ዕርዶቿን ልብ ብላችሁ ተመልከቱ፤
መጠበቂያ ማማዎቿን እዩ።
14ይህ አምላክ ከዘላለም እስከ ዘላለም አምላካችን ነውና፤
እስከ መጨረሻው የሚመራንም እርሱ ነው።
Copyright information for AmhNASV